ሻደይ ጨዋታ በዋግ

ሻደይ በጣም ያሸበረቀና የሚስብ የሴቶች በዓል ነው፡፡ የሻደይ ቃል የተወሰደው ከቅጠል ነው ይህንም ቅጠል ለዝግጅቱ በዓል ይጠቀሙታል በዓሉም በየአመቱ ነሃሴ 16-21 ይከበራል፡፡ በዓሉ ሃይማኖታዊም ታሪክ አለው በመሪያቸው አማካይነት ከሃይማኖታዊ ቦታ ከቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን ይሰበሰባሉ በትንሳኤውም ይወጣሉ በአራቱም አቅጣጫ ያሉ ቡድኖች ይገናኛሉ የምስጋና ዘፈኖችን ከቤተክርስቲያን ካደረሱ ቡኋላ ወደ ሌሎች አለማዊ ቦታ ይሄዳሉ፡፡ የሴቶች በዓል የሆነ ታሪክ ነው በዓሉም የሚዘጋጀው በባህላዊ ቀለማት ባሸበረቁ ልብሶችን ለብሰው ይውላሉ፡፡ በዓሉ የባህላዊ አልባሳትን አይነቶችና የሴቶችን ባህላዊ ዘፈን ውድድር ለማየት ምቱ አጋጣሚን ይፈጥራል፡፡ ጫወታቸውን ሲጀምሩ በአቅራቢያቸው ባለ ቤተክርስቲያን በሰላምና በጤና ለዝግጅቱ ስለመድረሳቸው ከሻደይ ቅጠል ቆርጠው ወደ ቤተክርስቲያኑ ስጦታ ይጥላሉ ቀጥሎም ለቀጣይ አመት በሰላምና በጤና እንዲያደርሳቸውይፀልያሉ ምስጋናም ያቀርባሉ ከዚያም ወደ ተከበረ ትልቅ ሰው ወይም መሪ በመሄድ ባህላዊ ዘፈኖችን ያቀርባሉ እናም ስጦታም ይቀበላሉ፡፡





ሻደይ ጨዋታ በዋግ
በ15/ በበዓሉ ዋዜማ/ ከሰዓት በኋላ ልጃገረዶቹ ወደ በረሃ ወርደው የሻደይ ቅጠል ይሰበሰባሉ፡፡ ሻደይ የሚሰበስቡበት አካባቢ ራቅ ያለ ከሆነ ወይም ዝናብ ካለ ወይም ገደላማ ከሆነ / ቅጠሉ በአብዛኛው በገደላማ አካባቢ የሚቅል ነው / ከወንድሞቻቸው ወይም ጎረቤት ካለ ጎረምሳ ይዘው ይሄዳሉ፡፡ ከዚያም የቻሉትን ያህል ይጥፋሉ፡፡ የቻሉ አሸንዳውን ማታዉኑ አሰርተው ያድራሉ፡፡ ካልተመቻቸው ደግሞ በማግስቱ ጠዋት ያሰራሉ ወይም ይሰራሉ፡፡ ሲዘጋጅም ራሳቸው ያዘጋጁታል፤ ካልቻሉ ደግሞ እህቶቻቸው ወይም እናቶቻቸው ያዘጋጁላቸዋል፡፡ በዚህ ጊዜ አልሰራም አይባልም፡፡ የሚልም ካለ ጥላቻው የመረረ ይሆናል፡፡ በ16 ጥዋት ቁርስ ከተበላ በኋላ በረሃ የሚሰማሩ ካሉ በረሃ ከተሰማሩ በኋላ ከሰኣት በኋላ እንደሚገናኙ ይነጋገራሉ፤ ወደ በረሃ የማይሄዱ እናቶቻቸው ጋ የሚቆዩም ይነራሉ ከሰዓት ለመገናኘት ይቀጣጠራሉ፡፡ ከሰዓት በኋላም ይገናኘሉ፡፡ ተጠራርተው ይሰባሰባሉ፡፡ ሲጠራሩ መሰባሰብ ሲጀምሩ ለቤት ስራ ማንም አያዛቸውም፡፡ ለክልክል የምትል እናት እንኳን ብትኖር ጎረቤቶቿ ጭምር አይንሽ ላፈር ይሏታል፡፡ ከተጠራሩም በኋላ በመንደሩ ካለ ግልጽ ሸንጎ/ቀዬ ላይ ይገናኛሉ፡፡ ሲጠራሩም ሁለት አይነት አካሄድ አለው፡፡ ከዚያም በአካባቢያቸው ወዳለ ደብር ይሄዱሉ / በአንድ ደብር አራት አምስት መንደር ሊኖር ይችላል/፡፡ የሁሉም መንደር ተጫዋቾች ደብሩ ላይ ይገናኛሉ፡፡ ወደቤተክርስቲያኑም የሚሄዱት አበባ ለመጣል ነው፡፡ በዚህ ጊዜ አበባ ጣሉ ይባላል፡፡ በመንግስት ሹምነት የሚታወቁ ሰው ካሉ፤ በእድሜ የገፉ የሃገር ሽማግሌ ወይም ምራቅ የዋጡ ሰው ካሉ ከመንደሩ እሳቸው ይመረጣሉ፡፡ ከቤተክርስቲያን መልስ መጀመሪያ የሚኬደው ወደነኚሁ ሰው ቤት ነው፡፡ እዚህም አበባ ይጥላሉ፡፡ እዚህም አበባ ጣሉ ይባላል፡፡ ወደቤተክርስቲያንም ሆነ ወደሹም ወይም በእድሜ ገፋ ያሉ የሃገር ሽማግሌ ቤት ሲሄዱ እንዲህ እያሉ ይጫወታሉ፡፡
			      ሻደይ ነሽ አሉ ሻደይ
				ሻደይ ነሽ አሉ በያገሩ

				አሽከር አበባዬ  . . . . . . .  አሽከር አበባ
				አሽከር አበባዬ  . . . . . . .  አሽከር አበባ
				
				ሻደይ ነሽ አሉ ሻደይ
ይህን እየተጫወቱ ቤተክርስቲያኑንም እያወደሱ ይጨፍራሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ቤተክርስቲያን የተገኙ የሃይማኖት አባት ወይም አቃቢት ወይም ማንኛውም ሌላ ሰው ይመርቋቸው፡፡ ‹‹ ተባረኩ፣ የከርሞ ሰው ይበላችሁ›› ብለው፡፡ በዚህ ጊዜ የሚሰጥ ነገር አይጠበቅም፡፡ በሹም ወይም በእድሜ ገፋ ካሉት ሽማግሌ ቤት አበባ ሲጥሉና ሲጫወቱ ግን የሚሰጥ ስጦታ ይኖራል፡፡ ከላይ ያየነውን ዜማ ከማለታቸው በፊትም እንዲህ እያሉ ከግቢው አጥር ላይ ሆነው ይዘፍናሉ
	አስገባኝ በረኛ . . . . . . . .አስገባኝ 
ከልካይ       . . . .     አስገባኝ 
እመቤቴን ላይ . . . . . . . አስገባኝ
ከልካይ  . . . . . . . .  . .አስገባኝ
እመቤቴን ላይ . . . . . . .. አስገባኝ
ከልካይ     . . . . . . . . . አስገባኝ
ይህን ከዘፈኑና ከተጫወቱ በኋላ ነው ከላይ ያያነውን የሚጫወቱት ወደ ሹም ወይም አንጋፋ የሃገር ሽማግሌ ቤት ሲገቡ፡፡ ከዚያም እንዱህ እያሉ ይዘፍናሉ፡-
	ሻደይ ነሽ አሉ ሻደይ
			አሽከር አበባዬ . . . . . . . . .አሽከር አበባ / 2 /
			አሽከር ይሙት/2/ ይላሉ የኔታ
			አሽከር አይደለም ወይ የሚሆነው ጌታ
እያሉ ይጫወታሉ፡፡ እዚህ ላይ ሽከር የሚባለው ሎሌ ቅጥረኛ ስለሆነ ሰው አይደለም፡፡ ልጅ ለማለት ነው፡፡ በድሮው ጨዋታ ግን ከላይ ያየነው ግጥም የመጨራ ሁለት ግጥሞች እንዲህ ተብለው ይዜሙ ነበር፡-
			አሽከር ይሙት/2/ ይላሉ የኔታ
				እርሶ አይሞቱም ወይ ያውም ዛሬ ማታ
የህ ግጥም በሁሉም የዋግ ምድር የተለመደ አይደለም፡፡ ወለህና ሐሙሲት አካባቢ ይህን ይጫወቱታል፡፡ ይህን ብለው የሚዘፍኑት አሽከር ይሙት ተብለው ተስድበው ሲለሚናደዱ ነው፡፡ ተሰዳቢዎቹ ግን የሃይል ምላሽ አይሰጡም፤ በባህሉ የሚፈቀድ ነውና፡፡ እንዲያዛ ከተጫወቱ በኋላ ስጦታ ይሰጣል፡፡ ገጠር ላይ እንደከተማው ገንዘብ አይደለም የሚሰጠው፡፡ እሚበላ የሚጠጣ ነበር የሚሰጠው፡፡ ያለው ከሆነ በእለቱ ይሰጣል፡፡ ማር ከሆነ ማር በጥብጦ ይሰጣል፤ እርጎ ካለው ደግሞ እርጎ ያቀርባሉ፡፡ በእድሜም በሃብትም የታወቁ ሰዎች ግን ብር ይሰጡ ነበር፡፡ ቀደን ሲል አንድ ብር አንኳ በጣም ብዙ ብር ነበር፡፡ በስተመዐረሻም እንዲህ ብለው ይዘፍናሉ፡- አስተሊለየ ለየ . . . . . . ስለል በየ /2/ እያሉ ይዘፍናሉ፡፡ ከዚያም ተመርቀው ወደሚቀጥለው ጨዋታ ይሄዳሉ፡፡ ሙሉ ስርዓቱ ይህን ይመስል ነበር፡፡ በማስከተል ደግሞ የድሮውና የአሁኑ ገጽታ እያስተያየን ያለውን ለውጥ እንመልከት፡
    አልባሳትና አለባበስ • የሕጻናት
  • ሕጻናት የፕሮቶኮል አለባበስ ብዙም አያስጨንቃቸውም፡፡ የለበሷትን ለብሰው/የተቀደደም ሊሆን ይችላል/ አሸንዳውን ማሰራቸውን አይተዉም፡፡ አዲስ ልብስ አልተገዛልንም ብለው ሳይሆን አሸንዳ አልተገዛልንም ብለው ነበር የሚያለቅሱት፡፡
  • መቀነት አያደርጉም
  • • በእድሜ ከሕጻናት ከፍ ያሉ
  • ለእጮኝነት የደረሱ ናቸው፡፡
  • ለአውደአመት ብቻ የሚወጣ የክት ልብስ ይኖራቸዋል፡፡
  • ልበሱ ከታጩ ከአማቶቻቸው የተሰጣቸው ሊሆን ይችላል፤ ካልታጩ ወላጆቻቸው ያለብሷቸዋል፡፡
  • ካልታጨች ለመታጨት አይን እንድትግባ ወላጆች ልብስ ይገዙላቸዋል፡፡ ልጄ ደርሳለች እንደማለትም ነው፡፡
  • ልብስ ካተገዘላት ‹‹ የእከሌ ልጅ እሚቆጥራት የሌለ›› ተብላ ትተቻለች
  • መቀነት ያስራሉ
  • • አዋቂ ሴቶች
  • ሙሉ ቀሚስ ይለብሳሉ፤ መቀነትም ያደርጋሉ፡፡
  • ጌጥና አጋጌጥ • ሕጻናት
  • ጆሯቸውን ይበሳሉ፡፡ ቢበሱም ለቀጣይ እንጂ በዚህ እድሜ ጠጆሮ ጌጥ አያደርጉም፡፡ ለጊዜው ግን ከቆርቆሮ ተሰራም ቢሆን ያደርጋሉ፡፡ከቀለበቷ ላይ ከጠርሙስ የተሰራ ድባ ይንጠለጠላል፡፡
  • • በእድሜ ከሕጻናት ከፍ ያሉ
  • የታጩና ያልታጩ የሚለይ ጌጥ አለ፡፡ የታጨችው ድባ፣ ጠልሰምና ማርዳ ታስራለች፡፡
  • ያልታጨችው ማርዳ ማርዳ አታስርም፡፡ ሻደይ ለት ግን መተጫጨት ስለሚኖር ሊከሰት ይችላል፡፡
  • ያገቡ ከእነዚህ ጋር የሚካተቱ አሉ፡፡ ግን መለያ አላቸው፡-
  • ከት ከእጃቸው ያደርጋሉ፡፡ አንድ ዱከት ነው የሚያደርጉት፡፡
  • ገባች ብዙ ያልቆየች ከሆነችና ካልወለደች አሁንም ማርዳ ታደርጋለች፡፡
  • መስቀል ያስራሉ፤ በአንገታቸው ዙሪያ፡፡
  • ሹከር የተባለ የጆሮ ጌጥ በላይኛ የጆሮ ክፍል ላይ ያደርጋሉ፡፡
  • • አዋቂ ሴቶች
  • ሁለት እጃቸው ላይ ዱከት ያስራሉ፡፡ ድሪና ከጥቁር ክር በተፈተሉ ድንብል ቀለበት ያደርጋሉ፡፡
  • እግር ላይ አልቦ ያደርጋሉ፡፡ ከብር የሚሰራ ነው፡፡ ሁለቱም እግራቸው ላይ ቁርጭምችሚት አካባቢ ያደርጉታል፡፡ አልቦ ለመግዛት የኢኮኖሚ አቅም ይወስን ነበር፡፡ ሃብት ያላቸው የሚገዙት ነበር፡፡
  • ድፍን ስሬት ላይ ሲደርሱ እነሱ ባህሉ በሚፈቅደው መሰረት ከእድሜ ጋር የተዋቸውን ጌጣጌጦች በአገልግል ለልጆቻቸው ያስቀምጡላቸዋል፡፡
  • ጸጉር አሰራር • ሕጻናት
  • ጸጉራቸው ን ስንመለከት ከመካከል ላይ ብቻ ቁንጮ ይሰራሉ፡፡ ያልደረሰ ከሆነ ቁንጮዋ ያልተሰራ፣ ለመቆንጠጥ የደረሰ ከሆነ ቁንጮዋ ትሰራለች፡፡ ከዚያ እናታቸው ቅቤ ይቀቧቸዋል፡፡
  • • በእድሜ ከሕጻናት ከፍ ያሉ
  • በሕጻንነት በተሰራው ቁንጮ ላይ ጋሜ ይጨመርበትና ጋሜና ቁንጮ ትሰራለች፡፡ ቅቤ ትቀባለች፡፡
  • • አዋቂ ሴቶች
  • አግብታ የወለደች ቅርድ ትሰራለች፡፡ ቅርድ የሚባለው ሙሉ ሹርባዋን ከተሰራች በኋላ መሃል ላይ በቁንጮ ምትክ / ቁንጮ ነበረበት ቦታ ላይ ከመሃል ላይ በክብ ቅርጽ ይላጫል፡፡ ትልቅ ሴት እየሆነች ስትሄድ መላጨቱ ይቀርና እያደገ ሄዶ ይደፍንና ከዋናው ሹርባ ጋር ተያይዞ ይሰራል፡፡ ስትደፍፍን ‹‹ ትልቅ ሆናለች›› ይባላል፡፡

  • ምንጭ፡- ዋግ ኽምራ ዞን ባህል ቱሪዝም አሸናፊ